ማዕከላዊ ስታትስቲክስ ኤጀንሲ ከሁሉም ባለድርሻ አካላት ጋር በጌትፋም ሆቴል የካቲት 17 ቀን 2009 ዓ.ም ባዘጋጀው የምክክር መድረክ ላይ በአራተኛው ዙር የህዝብና ቤቶች ቆጠራ መጠይቅ ላይ የመጨረሻ ማሻሻያ ለማድረግ የሚያስችል ግብአት ተሰባሰበ፡፡
በኢ.ፌ.ዲሪ ሕገ መንግሥት በኢትዮጵያ ህዝብና ቤት ቆጠራ በየ10 ዓመቱ እንደሚካሄድ በተደነገገው መሠረት አራተኛውን ዙር የህዝብና ቤቶች ቆጠራ ህዳር 10 ቀን 2010 ለማካሔድ ለቆጠራው የሚያስፈልገውን የካርታ ስራ ጨምሮ አስፈላጊው ቅድመ ዝግጅት በመከናወን ላይ ይገኛል፡፡
በምክክር መድረኩ ላይ የቅድመ ዝግጅቱ አንድ አካል የሆነው የቆጠራው መጠይቅም የመጨረሻ ማሻሻያ እንዲደረግበት ለተሳታፊዎቹ ቀርቦ ከተለያዩ ባለድርሻ አካላት አስተያየት ለማሰባሰብ ተችሏል፡፡
በውይይት መድረኩ ላይ በማዕከላዊ ስታቲስቲክስ ኤጀንሲ የስነ ህዝብና ቫይታል ስታትስቲክስ ዘርፍ ምክትል ዋና ዳይሬክተር አቶ አሳልፈው አበራ ስለ ቆጠራ ታሪክና ኢትዮጵያ በህዝብና ቤቶች ቆጠራ ስላላት ተሞክሮ ሰፋ ያለ ማብራሪያ ያቀረቡ ሲሆን በዝግጅቱ ተሳታፊ ከነበሩት ባለድርሻ አካላት መካከል ከተባበሩት መንግሥታት የሕዝብፈንድ (UNFPA) የተወከሉት ኮሊን ስኦፒዮ “የሕዝብ ቆጠራ መጠይቅ ዲዛይን መሠረታዊ መርሆዎች” (census questioner design fundamental principles) በሚል ርዕስ አለም አቀፍ የሥነ ህዝብና ቤቶች ቆጠራ መጠይቆችን አዘገጃጀት የሚያሳይ ሰፋ ያለማብራሪያ አቅርበዋል፡፡
ለአራተኛው ዙር ህዝብና ቤቶች ቆጠራ የተዘጋጀው መጠይቅ በአገሪቱ ውስጥ በሚገኙ ዘጠኝ ክልሎች እና ሁለት የከተማ አስተዳደሮች ውስጥ የእያንዳንዱን የቤተሰብ አባል ዝርዝር መረጃ ለማግኘት የሚያስችሉ ጥያቄዎችን ያካተተ መሆኑን ለመረዳት ተችሏል፡፡
በምክክር መድረኩ ላይ በመጠይቁ ውስጥ ስለተካተቱ ጥያቄዎች ምንነት ና አስፈላጊነት በማዕከላዊ ስታቲስቲክስ ኤጀንሲ የስታቲስቲክስ ኤክስፐርቶች አማካኝነት ሰፊ ማብራሪያ ተሰጥቶበታል፡፡
በምክክር መድረኩ ላይ የተሳታፊዎችን ትኩረት መያዝ ከቻሉ አስተያየቶች መካከልም የስደተኞችን መረጃ አያያዝ በተመለከተ የተነሳው ጥያቄ ሲሆን ከዚህ ርዕሰ-ጉዳይ ጋር በተያያዘም ስደተኛ ማነው?፣ ስንት አይነት ስደተኛ አለ?፣ ሀገር ውስጥ ከቦታ ቦታ የሚሰደዱ ሰዎች የመረጃ አሰባሰብ ሁኔታ ምን ይመስላል ? የሚሉ ጥያቄዎች ቀርበው ምላሽ ተሰጥቶባቸዋል።
የማዕከላዊ ስታቲስቲክስ ኤጀንሲ ባለሙያዎችም በተሳታፊዎች ለቀረቡ የተለያዩ ጥያቄዎች መልስ የሰጡ ሲሆን የቀረቡ ገንቢ አስተያየቶችንም በመቀበል መጠይቁን የተሟላ ለማድረግ በግብአትነት እንደሚጠቀሙባቸው አስረድተዋል።